ሀገሬ ቲቪ

አቢሲኒያ ባንክ 4.6 ቢሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን ገለጸ

አቢሲኒያ ባንክ በሀገሪቱ የተከሰቱ የጸጥታ ችግሮች እና የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ስራዎቹ ላይ ተጽዕኖ ቢያሳድሩበትም ካለፈው የሂሳብ ዓመት አንጻር የላቀ ውጤት ማስመዝገቡን ገልጿል ።

በ 2021/22 የሂሳብ ዓመት ካለፈው ዓመት አንጻር 127 በመቶ ጭማሪ በማሳየት ያልተጣራ 4.6 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማግኘት ችያለሁ ያለው ባንኩ በዚህም አጠቃላይ የሀብት መጠኑ 149.4 ቢሊዮን ብር ማድረሱን አስታውቋል ።

በተጠናቀቀው ሂሳብ ዓመት የብድርና ቅድመ ክፍያዎች መጠን 113.3 ቢሊዮን ብር መድረሱን ያስታወቀው ባንኩ በሁሉም የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ የሰጠው ብድር ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ48 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱ ተጠቁሟል ።

ባንኩ በተጠናቀቀው ሂሳብ ዓመት ያቀዳቸውን አብዛኞቹን ግቦች ማሳካት የቻለ ቢሆንም በሀገሪቱና በተለያዩ የዓለም ክፍሎች በተፈጠሩ የሰላም መደፍረሶች ሳቢያ ማስገባት የቻለው የውጪ ምንዛሬ ከአምናው መጠኛ ቅናሽ ማሳቱ ተገልጿል ። በቀጣይም የውጪ ምንዛሬ ገቢውን ለማሳደግ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር እየሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።

ባንኩ የዲጂታል ባንኪንግ አገልግሎቱን የላቀ ደረጃ ለማድረስ ከ ቪዛ ካርድ ጋር በመተባበር አዲስ ካርድ የሚያወጡ ባለእድለኛ ደንበኞችን ወደ ኳታር ለመላክ የጀመረውን ዘመቻ በማጠናቀቅ አራት እድለኛ ደንበኞችን ሙሉ ውጪ በመሸፈን ወደ ኳታር የሚበሩበትን ቲኬት አስረክባል።

በዮሴፍ ከበደ
2022-11-28