ሀገሬ ቲቪ

የበርካታ አሜሪካውያን ምርጫ የኾነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በበርካታ አሜሪካውያን ዘንድ የሚመረጥ አየር መንገድ መሆኑን አንድ ሪፖርት አመላከተ።

ሲምፕል ፍላይት የተባለ ድረ ገፅ እንዳስነበበው እ.ኤ.አ 2022 ከጃንዋሪ ጀምሮ ባሉት ሰባት ወራት ብቻ ቀላል የማይባል ቁጥር ያላቸው ተጓዦች የኢትዮጵያ አየር መንገድን መርጠው ተጉዘዋል ብሏል ።

መረጃው የፈረንጆቹ 2022 ከገባ በ7 ወራት ውስጥ ብቻ 147,000 መንገደኞች የኢትዮጵያ አየር መንገድን በመጠቀም ወደተለያዩ ሀገር መጓዝ መቻላቸውን አጋርቷል ።

አየር መንገዱ በ2019 ከ 396 ሺ በላይ የ አሜሪካ መንገደኞችን ያጓጓዘ ሲሆን በ 2020 222 ሺ እንዲሁም በ 2021 332ሺ መንገደኞችን ከአሜሪካ ወደ ተለያዩ የአለማችን ክፍሎች አጓጉዟል ።

አየር መንገዱ በ 2022 ያጓጓዛቸው መንገደኞች ካለፉት አመታት ጋር ሲነጻጸር መጠነኛ ቅናሽ ያሳዩ ቢሆንም በዐለማችን የተከሰተው የኮሮና ቫይረስ እንዲሁም የሰላም መደፍረሶችን ተቋቁሞ በ 2022 ይህን ያህል መንገደኞችን ማጓጓዙ አሜሪካ በብዛት ከምትጠቀማቸው የ አፍሪካ አየር መንገዶች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት እንዲቀመጥ አድርጎታል።

ከ ዩናይትድ ስቴትስ ከሚነሱ አስር የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላኖች ውስጥ አራቱ መዳራሻቸው አዲስ አበባ መሆኑን ያመለከተው መረጃው ቀሪ ስድስቶቹ ደግሞ ወደተለያዩ ሀገራት የሚበሩ ናቸው ብሏል።

አየር መንገዱ ከሚያጓጉዛቸው መንገደጎች 233 ሺ የሚጠጉት በቀጥታ ከአሜሪካ ወደ አዲስ አበባ የተጓዙ ሲሆን 40 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ አዲስ አበባ በማረፍ ወደተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ጉዞ ማድረጋቸውን መረጃው አመልክቷል ።

መነሻቸውን ከ አሜሪካ በማድረግ ወደ ደቡብና ምስራቅ አፍሪካ መጓዝ ከሚፈልጉ መንገደኞች ውስጥ 70 በመቶው የ ኢትዮጵያ አየር መንገድን እንደሚጠቀሙም በመረጃው ተጠቅሷል ።

የአፍሪካዊያን ኩራት በመሆን በተለያዩ ጊዜያት ዐለም ዓቀፍ ሽልማቶች የሚበረከቱለት የ ኢትዮጵያ አየር መንገድ መዳረሻ ሀገራቶችን ብሎም የደንበኞችን ቁጥር ለማስፋት አዳዲስ ስራዎችን እየሰራ ይገኛል ።

አየር መንገዱ ከሚያመላልሳቸው ተጓዦች በተጨማሪ የ እቃ ጫኝ አውሮፕላኖች ቁጥርን በማሳደግ ላይ የሚገኝ ሲሆን በ2027_ 25 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ለማግኘት አቅዶ እየሰራ መሆኑንም አስታውቋል ።

በዮሴፍ ከበደ
2022-11-29