የብሄራዊ ደም ባንክ በህዳር ወር ብቻ ከ15ሺሕ በላይ ከረጢት ደም ሰበሰብኩ አለ፡፡ በሰሜኑ የሀገራችን አካባቢ የተነሳውን ጦርነት ተከትሎ በተለያዩ አካባቢዎች የሰው ህይወት ላይ ጉዳት እየደረሰ መሆኑ አይዘነጋም፡፡ ይህንኑ ተከትሎ የብሄራዊ ደም ባንክ የደም እጥረት እንዳያጋጥም አስቀድሞ የተለያዩ ስራዎችን በመስራት “ደሜን ለመከላከያ ሰራዊት”በሚል መሪ ቃል የደም ማሰባሰብ መርሀ ግብር ማዘጋጀቱ ይታወሳል፡፡ በዚህ ንቅናቄ በህዳር ወር 15 ሺሕ 286 ከረጢት ደም መሰብሰቡን በብሄራዊ ደም ባንክ አገልግሎት የደም ለጋሾች ዘርፍ አገልግሎት ዳይሬክተር ዶ/ር ተመስገን አበጀ ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ እና በክልሎች ከበቂ በላይ የሚባል የደም ክምችት መኖሩም ተሰምቷል፡፡ ከጦርነት ቀጠና ውጪ የሆኑት የደም ባንኮች እየሰሩ በመሆናቸው ለተጎጂዎች ተደራሽ ይደረጋሉም ተብሏል፡፡ ከሚሴ፣ወልዲያ እና ደሴ የደም ባንኮች አገልግሎት መስጠት አቁመዋል፡፡ ንብረት ላይ ጉዳት የደረሰባቸው የደም ባንኮችን የማቆቆም ስራ ይሰራልም ተብሏል፡፡
በሀገሬ ቲቪ
2021-12-10
